Sheik Husen Gibreel
Contents | ማውጫ

ሸህ ሁሴን ጅብሪል ትንቢት ፡ ጥንት አጀማመሩ ታሪክ

The Origion of Sheik Hussen Gibril

        ትንሽ ጠንከር ፡ በል ይኑርህ እውቀት
        ተጠንቅቀህ ስማን ፡ እንዳትሳሳት
        እኛ መላይኮች ፡ ነን አናውቅም ውሸት
        ተልከን ነው ፡ እንጂ እኛ አናዝበት
        ይሄንን ነግረውኝ ፡ ስንሰናበት
        ዋሪዳው መጣና ፡ ቆይ አለኝ አመት
      

ጌታው ሸህ ሁሴን ጅብሪል ፡ ፍርዱ እንደት እንደጀመራቸው ፡ ምን ምን እንዳጋጠማቸው ፡ ዘርዘር ባለ መንገድ አስቀምጠውታል ፣ አንድ አንዱ ነገር ተመወሳሰቡ የተነሳ ፡ ግጥሙን መከታተሉ ፡ ከማስረዳቱ ይቀላል።

بِسْمِ اللَّهِ الرَّحْمَنِ الرَّحِيم
  ሰው ብዙ ያወራል ፡ ፈጥሮ በግምት
  መቼም በኒ አደም ፡ ለወሬ አይታክት
  ጥቂት ፍንጭ ካየ ፡ ትንሽ ምልክት
  ያችን ይይዝና ፡ እንደ ሽልማት
  አብሮ እንደነበረ ፡ ባይኖቹ እንዳያት
  ምንም ሳይሰማው ፡ የፍርሃት ስሜት
  ሰው ምን ይለኝ ሳይል ፡ ቁሞ ከሰው ፊት
  ውሸቱን ያወራል ፡ ሰዎች እያዩት
  ምን ተብሎ ይጠራል ፡ የዚህ ሰው አይነት?

  እኔ ልንገራችሁ ፡ ስለኔ ሂወት
  ልታምኑም ላታምኑም ፡ አላችሁ መብት
  ትንሽ ከበድ ይላል ፡ በቃል ሲያወሩት
  ገና ትንሽ ሁኘ ፡ በስድስት አመት
  ተጫወቼ ሳልጠግብ ፡ እንደ ህፃናት
  ገና ለሚመጣው ፡ መሰለኝ ታይቶት
  ግን ትንሽ ጠብቀን ፡ ሲለኝ ሰማሁት

  ትንሽ ጠንከር በል ፡ ይኑርህ እውቀት
  ተጠንቅቀህ ስማን ፡ እንዳትሳሳት
  እኛ መላይኮች ነን ፡ አናውቅም ውሸት
  ተልከን ነው እንጂ ፡ እኛ አናዝበት
  ይሄንን ነግረውኝ ፡ ስንሰናበት
  ዋሪዳው መጣና ፡ ቆይ አለኝ አመት
  ጫትክን እየቃቃምክ ፡ ሳትወሳለት
  ተዱሮ ሰዎች ጋር ፡ ተጫወት ተቤት
  እኔም ኸልዋ ፡ ገባሁ ቆየሁ አንድ አመት

  አላህ ያሳየኝን ፡ ተማምኜበት
  ሙእጅዛ ስጠብቅ ፡ ታላህ ምልክት
  መነጥር ተሰጠኝ ፡ ታላህ ግምጃ ቤት
  ማንም ሰው ያላያት ፡ ማንም ያልነካት
  አበጥራ የምታይ ፡ ሸክ የሌለባት

  ባህር አይጋርዳት ፡ ጎራ አይከልላት
  ቢደበቅ ቢሸሸግ ፡ የማያመልጣት
  አታረጅ አትዝግ ፡ ወይ አትማራት
  አላህ በጥበቡ ፡ በጁ የሰራት
  ለወደደው ባሪያው ፡ አዝኖ የሚሰጣት
  እንግዲያ እውቀት የለኝ ፡ የምኮራበት
  እንደቃልቶቹም ፡ የለኝም ትምህርት
  እድሜየም ትንሽ ነው ፡ እኔ በዛ ወቅት
  ለአላህ ልዩ ነገር ፡ ምን አድርጌለት፧

  አዝኖልኝ ነው እንጂ ፡ ረበል ኢዘት
  ገና ሲወጥነኝ ፡ ሲፈጥረኝ ከጧት
  በጁ ስለሆነ ፡ መስጠት መቀማት
  ለፈለገው ቢሰጥ ፡ ማንስ ጠይቆት
  ሰው አይረዳውም ፡ ይሄን ሲነግሩት
  አንዳንዱም ከብዶት ነው ፡ አንዳንዱም ቅናት

  መነጥሯ እኔ ጋር ፡ አለች እስክሞት
  ዝም ብየ እንዳይመስልህ ፡ የምወሻክት
  የልጅ ልጅ ይመጣል ፡ የሚረክባት
  ከሞትኩኝ በኃላ ፡ ከብዙ አመታት
  ሰው እንዳይታለል ፡ እንዳይሳሳት
  ተቀኝ ጉንጩ ላይ ፡ አለው ምልክት
  የሆነች ነገር ናት ፡ እንደ ኪንታሮት
  በጣም ትንሽ ሁና ፡ ደመቅ ያለችናት
  መልከ መልካም ልጅ ነው ፡ ደስ የሚል ሲያዩት
  ቅንድቡ ግጥም ነው ፡ ያይኑ ሽፋሽፍት
  እራሱን ያመዋል ፡ ቀንና ሌሊት
  ሲቋደስ ብቻ ነው ፡ የሚበርድለት

  አፍንጫው ቀጥ ያለ ፡ የአረቦች አይነት
  ፊቱ ወለል ያለ ፡ እንደ መስታወት
  የቀማመሰ ነው ፡ ተዘመኑ እውቀት
  ማንበብ ግን ይወዳል ፡ የቁርዓን ዓያት
  ፍርድ እንደኔ አይፈርድም ፡ ህልሙ ግን አይስት

  ሰው ዝምብየ ፡ መስሎት የምቀሳፍት
  ፍርድ እየፈረድኩኝ ፡ ስናገር ትንቢት
  ግጥሙ ተጥፎልኝ ፡ ነው እያየሁት
  በወርቅማ ቀለም ፡ በነጭ ወረቀት
  ጥፌው እንዳይመስልህ ፡ ተራሴ አንደበት
  መስሎህ ተጠራጥረህ ፡ እንዳትሳሳት
  እኔ እንኳን እራሴ ፡ ባይኔ እያየሁት
  ማመን ያቅተኛል ፡ ጉድ አጃይበት
  ለቃልቾቹማ ፡ ከባድ ነው በውነት
  ግን አላህ ተሻልህ ፡ የለም የሚያቅት
  እኔ ምን ልነግርህ ፡ እራስህ ገምት

  መቸም ተቆጥሮ አያልቅ ፡ የጌታችን ኸይር
  ማጀቱ ሰፊ ነው ፡ የአላህ ሚስጥር
  አላህ ያሳየኝ ፡ እስቲ ልናገር
  ተሰጠኝ በኃላ ፡ ያንን መነጥር
  አለሙን አየሁት ፡ ተዳር አስተዳር
  አንዳትሸክከኝ ፡ እንዳትጠረጥር
  ውሽት እንዳይመስልህ ፡ የምልህ ነገር

  ንጉስ እየፈራን ፡ ሳይጠላን አሽከር
  ውስብስብ ነበረ ፡ ብዙ የሚያስቸግር
  የሚያሾፍም ነበር ፡ የሚስቅ ናኪር
  ዝምብየ መስሏቸው ፡ የምቀባጥር
  በጣም ተደፋፈርን ፡ ታንዳንዶችስ ጋር
  አፍ አውጥተው ፡ ዟሂር ይሰድቡኝ ጀመር
  እንደነሱ እስላምነኝ ፡ አይደለሁ ካፊር
  በእስላም ቀጥፎ ፡ ማውራት ዋሽቶ መናገር
  ከባድ ነው ፡ ቅጣቱ በሰማይ በምድር
  ይሄነን አውቃለሁ ፡ ምንም ባልማር
  ይሄን ህግ ፡ አልጥስም ምንም ብዳፈር

  ወዲያው ስሜ ፡ ታውቆ ሽዋና ሃረር
  እኔም በማስታውት ፡ ፊቴን ሳሳምር
  መደዱ ቀጠለ ፡ የጌታችን አምር
  ንጉሶች ፈለጉኝ ፡ ሃፍታምም ታጅር
  ምን ያውቅ ፡ ይሆን ተብሎ ምን ልዩ ነገር
  ጠንቋይ መስያቸው ፡ ስር የምቆፍር
  የምፈራው መስሎት ፡ የማወራ አሽሙር

  አፄ ቴዎድሮስን ፡ አግኝቸው ነበር
  አንድ የሚያሳስበው ፡ ነበረው ሚስጥር
  ተንግሊዞቹ ጋር ፡ ባለው ክርክር
  ትንሽ ልጅ ነው ብሎ ፡ ሳይንቀኝ በክብር
  ተሚወያዩበት ፡ አስጠራኝ ተደብር
  እኔም ተናገርኩኝ ፡ ፍርዱን በዝርዝር

  ችሎታው የለኝም ፡ አንተን ለመምከር
  አንተም አትመለስ ፡ ታስበው ነገር
  አገርክን ወዳጅ ነህ ፡ ጨካኝ ነህ ተምር
  እንግሊዝ አያውቅም ፡ ይሄንን ሚስጥር
  እንግሊዞች ላንተ ፡ ያስባሉ ሸር
  ያበሻ መኳንንት ፡ ለእንግሊዝ ሲያብር
  ማጥቃት አንኳን ባትችል ፡ የእንግሊዝን ጦር
  መጨረሻው አንኳን ፡ ነገሩ ባያምር
  በሚያቀርቡት ሃሳብ ፡ አትደራደር

  እጅህን እንዳትሰጥ ፡ ህዝቡ እንዳያፍር
  ጀግንነት ተገምዶ ፡ ባንተ ይቋጠር
  መቸም ሞት አይቀርም ፡ ስምህን አሰር
  ጠቅላላ ዙሪያውን ፡ ባበሻ ምድር
  ላገሩ ሞተላት ፡ ይበልህ አገር
  ሸሂድ ትሆናለህ ፡ ስትገባ ተቀበር
  ይሄነን ስነግረው ፡ ፊቱ አለ ቅይር
  እንደ አንበሳ አገሳ ፡ ሆነ እንደ ነብር

  ድሮም አይፈልግም ፡ ስሙ እንዲሰበር
  ቴዎድሮስ ሞት አይፈራም ፡ ይጠላል ነውር
  ማንንም ሳይፈራ ፡ ፊቱን ሳያዞር
  በጁ ታሪክ ሰራ ፡ አጃኢብ ታአምር
  ተዚህ በላይ ደፋር ፡ አለ ወይ ባገር

  ዩሐንስ አስጠራኝ ፡ አባቴን ሳይቀር
  መቶ አመት ያለፈው ፡ አዛውንት ነበር
  መሄድ ስለማይችል ፡ መራመድ በእግር
  በእንጨት ሰው ወሰደው ፡ ተረዳድቶ አገር
  ቁረብ ተባለና ፡ መልሱን ሲናገር
  መስራት ትችላለህ ፡ የሻህን ነገር
  ይቆርባል ብለህ ግን ፡ እንዳትጠረጥር
  እኔንም ብትገለኝ ፡ ልጄንም ብታስር
  ሃይማኖታችንን ፡ እንደማንቀይር
  ይሄንን ልንገርህ ፡ በግልጽ በዟሂር

  ብሞት ይሻለኛል ፡ ዛሬን ባላድር
  ሻሂድ ሁኖ መሞት ፡ ለእስላም ልጅ ነው ክብር
  ላኢላሃ ኢል ፡ አሏህ ፡ አላሁ አክበር

  አንድ ተራ ሙስሊም ፡ ይሄን ሲናገር
  እስላም ይጥፋ ተብሎ ፡ ባበሻ ምድር
  ዑለማው ቃልቻው ፡ ሲደነጋገር
  በዛች መጥፎ ሰዓት ፡ በዛች በምትመር
  ህጉን መቃወም ነው ፡ ንጉሱን መድፈር

  እንደ ስልጣን የለም ፡ ቆሻሻነ ነገር
  እስላም ይጥፋ ተብሎ ፡ አዋጅ ሲነገር
  ጠቅላላ በድፍን ፡ ባበሻ ምድር
  በዩሐንስ ትእዛዝ ፡ በዘረጋው ሽር
  ላይሳካ ጉዳይ ፡ አዋጁ ላይሰምር
  አንድኛው ሊገደል ፡ አንዱ ሲታሰር
  በእስላም ይስቅ ፡ ነበር ያበሻ ኩፋር
  ያአላህ ባሪያ ሲሞት ፡ የጀሊል አሽከር

  ዩሐንስ ኣበዛው ፡ አለፈ ድንበር
  ለኔና ላባቴ ፡ መግደል ሲሞክር
  ምንም ሳናጠፋ ፡ ሰው ሳናስቸግር
  ተይዘን ስንሄድ ፡ ጉድ እያለ አገር
  በተወለድንበት ፡ ባደግንበት ሰፈር
  አላህን ለመንነው ፡ አልቅሰን ተምር
  ለኛ ያሰበው ሞት ፡ ወደሱ እንዲዞር

  ብዙ ጊዜ ፡ ሳይቆይ ፡ ሳይውል ሳያድር
  ተመትቶ ወደቀ ፡ በድርቡሽ ብትር
  ተለይቶ ራሱ ፡ ታንገቱ እስቲበር
  ተጦር ላይ ተሰክቶ ፡ ራሱ እስቲዞር
  በደርቡሾች ግዛት ፡ በሱዳን አገር
  መለየት ይችላል ፡ አላህ ማበጠር
  የተደባለቀን ፡ ለይቶ ማንጠር

  የሐንስ የእስላሙን ፡ አንገት ሲቆጥር
  ስንት እንደገደለ ፡ ስንት እንደሚያስር
  አላህ ክፈል አለው ፡ የእስላሙን ብድር
  የሙስሊሞቹ ደም ፡ ፈሶ እንዴት ይቅር
  በሰፈርካት ቁና ፡ አንተም ተሰፈር
  ፍርዱ ከባድ ነበር ፡ ጌታችን ቃዲር
  ተዚህ ላይ ያበቃል ፡ የዩሐንስ ዐምር

  ምኒሊክ ፈተነኝ ፡ በብዙ ነገር
  ጠንቋዩን ሰብስቦ ፡ ዘግቶ በአንድ አጥር
  ሊገደሉ ተብሎ ፡ ህዝቡ ሲሽበር
  እኔንም አስጠራኝ ፡ ላከብኝ አሽከር
  እሽ ብየ ሄድኩኝ ፡ ትዛዙን ላከብር
  አላህ የሻው ነገር ፡ ምን ጊዜም አይቀር
  ጅን መቶት ተብሎ ፡ ህዝብ ሲነጋገር
  መልሱን ነገርኳቸው ፡ አድርጌ ዝርዝር
  ቃሌ ሳይዛነፍ ፡ ሳልደናገር
  አላሳፈረኝም ፡ ሀሊቁል ጀባር
  እንግዲያ ሌላማ ፡ ምን አለኝ ቀድር

  የፈረድኩት ነገር ፡ አንዷም ሳትቀር
  እየደረሳቸው ፡ ያምኑብኝ ጀመር
  ስድቡም ቀነሰልኝ ፡ የሰው ቁጥር

  አላህ ሲያሳምረው ፡ ሰው እጣው ሲወጣ
  አመት አስቀመጠኝ ፡ ተኸልዋ ሳልወጣ
  ወዲያው መናብ አየሁ ፡ አንበሳ ሲመጣ
  ነብር ከኋላየ ፡ ጅብ ከፊቴ መጣ
  ሁለቱ ሲጣሉ ፡ ጅቡ ደነገጣ
  ነፍሴን አውጭኝ ብሎ ፡ ሮጦ አመለጣ
  ግመል የጋለበ ፡ የሆነ ስው መጣ
  ከዛፍ ስር ሆነና ፡ አስሯት ተቀመጣ

  ነብሩን እያሻሸ ፡ አንበሳው ላይ ወጣ
  ይታገለው ጀመር ፡ እየተቀናጣ
  ይበሉታል ብየ ፡ ልቤ ደነገጣ
  ነብሩ በረረና ፡ ወደ ሰማይ ወጣ
  አንበሳው መሬቱን ፡ ጫረና ረገጣ
  እሱም በሮ ሄደ ፡ ወደ ሰማይ ወጣ
  ሰውየው ሂድ አለኝ ፡ ለቀቀኝ በነጣ
  ግመሊቱ ቀረች ፡ ተዛው ተቀምጣ

  ሰውየው ከወንዙ ፡ ውሃ ቀድቶ ጠጣ
  ትንሽ ቆየት ብሎ ፡ ከዛፉ ላይ ወጣ
  ተዛፉ ቀንዘሎች ፡ ትንሽ ቆራረጣ
  በጁ አፍተለተለው ፡ አንሚጥል ጣጣ
  እንዷን መዘዘና ፡ ወደኔ እየመጣ
  ግመሏ ታይ ነበር ፡ ወደ ላይ አንጋጣ
  እየመጣ ሳለ ፡ አለው እንደማዳጣ
  ሁሴን ብሎ ጠራኝ ፡ ወደኔ እየሮጣ
  እኔም ለበይክ እልኩኝ ፡ ሰላምታ ልስጣ
  ተቀበል እንካ አለኝ ፡ ይሄ ነው ያንተ እጣ
  ተቀብየ ሳየው ፡ የስጠኝን እጣ
  ተራስ የሚለበስ ፡ ይመስላል ባርኔጣ
  በውስጧ ቀይ ናት ፡ ሲያዩዋት ተገልብጣ
  ሰፋ ትለኛለች ፡ ትንሽ ተለጥጣ
  ተራሴ አጠለቅኳት ፡ ድምጧ ግን ሲንጣጣ

  መናቡን አይቸ ፡ ለሰው ሳላወራ
  በሰባተኛው ቀን ፡ መጣ አንድ ቀብራራ
  መሰንቆና ዋሽንት ፡ በጁ ይዞ ጭራ
  ከኔ ጋር አደረ ፡ ጫት ሲቅም ሲያወራ
  ማሲንቆ እየመታ ፡ ሲዘፍን ሲያቅራራ
  ዶሴ ተሸክሞ ፡ መጣ አንድ ገታራ
  እሱም ቁጭ ብሎ ፡ ትንሽ አወራራ

  እኔም ዝም ብዬ ፡ እያቸው ነበራ
  ተላይ ድምጽ ሰማሁ ፡ ቁርአን እየቀራ
  ዙሬ ማየት ጀመርኩ ፡ በቀኝም በግራ
  ተሩቅ በሮ መጣ ፡ አንድ ነጭ አሞራ
  ፊቱ ሰው ይመስላል ፡ ክንፉ እንደ ጆቢራ

  ተትክሻ የላይ ፡ አረፈ ሰፈሩ
  ተኔ ላይ ቁጭ ብሎ ፡ ሌላ አሞራ ጠራ
  እሱም ብዙ አልቆየም ፡ መጣ እየበረራ
  ሽልምልም ያለ ነው ፡ ልክ እንደ ባንዲራ
  ሁሴን ጅብሪል ብሎ ፡ በስሜ ተጣራ
  እኔ መሄዴ ነው ፡ ወደ ሌላ ስፍራ
  ከኔ ጋር ለቀረው ፡ ለዛ ለጆቢራ
  ብሎ ተናገረው ፡ ሁሴንን አደራ
  እንዳትለይ ከሱ ፡ በሄደበት ስፍራ
  መቁረጫ ጎራዴ ፡ መክተፊያ እንደካራ
  ጫፏ ሹል የሆነች ፡ የብረት ከዘራ
  በእጄ አስያዘኝና ፡ በሮ ሄደ ዙራ

  አላህ ሲያመቻቸው ፡ ነገሩ ሲሰላ
  በስምንተኛው ቀን ፡ ጫት ስንቅም ስንበላ
  እየተሟሟቀ ፡ ራምሳው ቢስሚላ
  ከውጭ ሰው መጣ ፡ መልኩ ያለቀላ
  ብሎ ተናገረ ፡ ሁሴን ቡኑን አፍላ
  ያስብከው የልብህ ፡ ሃጃህ እንዲሞላ

  እኔም እየከደምኩ ፡ ቡናውን ሳፈላ
  ይመርቁኝ ጀመር ፡ ሁሉም በጠቅላላ
  እኔም አሚን አልኩኝ ፡ ሃጃዬ እንዲሟላ

  ተመጅሊሱ ገባ ፡ ተውጭ መጥቶ ሌላ
  እሱም መራረቀኝ ፡ እያለ ማሻአላ
  ብዙ ሰው ይውደድህ ፡ አንተም ሰው አትጥላ

  ስምንት ቀን አደርኩ ፡ ሳትናገር አፌ
  የቤቱን ግድግዳ ፡ ግንዱን ተደግፌ
  ፊቴን እየታጠብኩ ፡ እንዳይመጣ እንቅልፌ
  ጩኸት እንዳልሰማ ፡ ጀሮየን ወትፌ
  የሸሆቸን ኪታብ ፡ በጎኔ ታቅፌ
  እንዲቀመጡበት ፡ ጋቢዬን አንጥፌ

  ሱሪዬንም ትንሽ ፡ ወደ ላይ አጥፌ
  ጭቃ እንዳይነካብኝ ፡ በደንብ ከፍክፌ
  ብዙ እንደሰራ ሰው ፡ ላቤን አንጠፍጥፌ
  ጉዝጓዝ ተጎዝጉዞ ፡ አሩቲና ጨፌ
  አይገርማችሁም ወይ ፡ ሳልደክም ማትረፌ?
  ፡፡፡፡፡፡፡፡፡	፡፡፡፡፡፡፡፡፡
  ሸሆች ሽማግሌዎች ፡ ትላልቅ አበጋር
  ስማቸው ገናና ፡ የታወቁ ባገር
  መናቡን ለነሱ ፡ ነግሬአቸው ነበር
  መናቡን ፈሰርነው ፡ አንተ ስትናገር
  ህልም እንደፈቺው ነው ፡ ይባላል በኛ አገር
  ጠጅ እየቀማመስክ ፡ ጫት ስትቅም ስትኖር
  ከስልጣን ላይ ያለ ፡ ባልጋም ላይ በወንበር
  ሁሉም ይፈራሃል ፡ እንዳትጠራጠር
  ሁሉም እየፈራህ ፡ በዋልክበት እደር
  ስላንተ ይወራ ፡ ስላንተ ይነገር
  በቆላም በደጋ ፡ በከተማም ገጠር
  የረገምከው እርጉም ፡ የመረቅከው ይመር
  በሄድክበት ይቅናህ ፡ አያጋጥምህ ችግር
  ጠላት እንዳይነካህ ፡ ጎራዴ እንካ በትር
  ሃሲድ የምትመታ ፡ ትላልቅ ሹም ሳይቀር
  ጀባ ብለንሃል ፡ እነሆ በዟሂር
  አሚን ማለት ብቻ ፡ ሆነ የኔ ነገር

  እየገባኝ መጣ ፡ ነገሩ ቆየ እንጅ
  አንድ ነገር ሲቆይ ፡ አየ ሲያሰለች
  አላህ ታደረገኝ ፡ ለክልቁ ወዳጅ
  ጫቴን እየቃቃምኩ ፡ እየጠባሁ ጠጅ
  ማሲንቆ እየመታሁ ፡ ልወዛወዝ እንጅ
  በጭራ በዋሽንት ፡ ሰው ባልነካው በጅ
  ለሁሉ እንዲጠቅም ፡ ዱዓው እንዲበጅ
  ዱአችን ይሰማ ፡ ከጌታችን ደጅ
  ሁል ጊዜም ለማኝ ነው ፡ የዱዓ ነጋጅ
  የኸይር ዛፍ ሲተክል ፡ ይውላል ሲያበጅ
  ፍሬው አይቀንስም ፡ ይጨምራል እንጅ

  ስጦታው ይገርማል ፡ ሃሊቁ ረህማን
  አናወራዋለን ፡ ምን አስደበቀን
  ግልጥ እንዲሆንለት ፡ ብለን ነው ህዝቡን
  ስንት መጥፎ ነገር ፡ አላህ አሳየን
  በጣም የሚያስጠላ ፡ የሚዘገንን
  ምን እንሆን ነበር ፡ ያን ቢያሸክመን
  የሰጠኝን ይዤ ፡ ልበል ተመስገን
  ያልጣመው ይሳደብ ፡ ያመነም ይመን

  ጥቁር ጭራ ፡ ይዘን ድቢ እየመታን
  ሃሲድ እንዳይነካን ፡ አውሊያ እየጠራን
  አምስት ወቅት ሶላት ፡ እየሰጋገድን
  ማር ተበጥብጦልን ፡ ጠጅ እየጠጣን
  ሰው ያልነካው እጣ ፡ ጀሊሉ ሰጠን
  መጭውን አየነው ፡ ጉድ አጃኢቡን

  ለሰው ይመስለዋል ፡ ያወራሁ ውሸት
  አያደናገርኩት ፡ እያታለልኩት
  የግጥም አድርጌ ፡ ፍርድ ስፈርድለት
  አዳምጠኝ ልንገርህ ፡ ሚስጥሩን በእውነት
  አለም ስትስቅብኝ ፡ እኔም ሳቅኩባት
  ታለፉች በስተቀር ፡ ያለን በሂወት
  ሳለፉ ሳልደክም ፡ ምንም ሳልታክት
  ተከትቦ አየዋለሁ ፡ ስሙን ወደፊት
  በወርቅማ ቀለም ፡ በነጭ ወረቀት
  ይሄ ስጦታ ነው ፡ ታላህ ራህመት
  ገና ሳይፈጠር ፡ ሳይኖር በሂወት
  ስሙን ይነግረኛል ፡ ማን እንደሚሉት
  ታዲያ ሰው አይገባው ፡ ይሄን ሲነግሩት
  እንዲያው ዝም ብየ ፡ ማወራ መስሎት
  ዝምበል ሲሉኝ ነው ፡ የምወሻክት

  ምን አስለፈለፈኝ ፡ ሊታይ ወደፊት
  እንደዚህ ነው ፍርዱ ፡ መሆን ያለበት
  ባይኔማ ከታየኝ ፡ ቁጭ ብሎ ተፊት
  እያየሁት አይደል ፡ ምኑን ፈረድኩት
  ስር ሲምስ የሚያድረው ፡ ጠንቋይ በሌሊት
  ወዶ መሰለህ ወይ ፡ ነው እንጅ ጨንቆት
  ሰዎች እንዳያዩት ፡ እንዳይነቁበት
  ስንት ሰው ጠይቆ ፡ ስንት ሰው ነግሮት
  ያውም ካጋጠመው ፡ ከተሳካለት
  ለውን አሳምኖ ፡ ገንዘብ ለማግኘት
  ሳወራህ አዳምጠኝ ፡ እንዳትታክት
  አውሰልስለውና  ፡ እስኪ እሰብበት
  በኔና በነሱ ፡ ያለው ልየነት
  ብዙ አያስቸግርም ፡ ይሄን መገመት

  ከቤቴም ቁጭ ብየ ፡ መንገድም ብወጣ
  ምግብ እየበላሁ ፡ ወይ ቡና ስጠጣ
  ወይ ሱብሂ ሰግጄ ፡ ገና ጣይ ሳይወጣ
  ደስ ብሎኝ ብቀመጥ ፡ ከፍቶኝም ብቆጣ
  ሲጋፋ አየዋለሁ ፡ መሿለኪያ ሲያጣ
  ተልባ እንደተቆላ ፡ ከፊቴ ሲንጣጣ
  ስሙን ይነግረኛል ፡ ዋሪዳው ሲመጣ
  ምንድን እንደሚሆን ፡ የዛ የሰው እጣ
  ገና ሳይወለድ ፡ ከዱንያ ሳይመጣ
  የሚያገኝም ቢሆን ፡ ወይንም የሚያጣ

  ሰካራምም ቢሆን ፡ መጠጥ የሚጠጣ
  ስልጣንም አግኝቶ ፡ ከወንበር ቢወጣ
  ተይዞም ቢታሰር ፡ ተገሎም ቢቀጣ
  በቅሎ እንኳን ብትጥለው ፡ ሩጣ ፈርጥ ጣ
  አላህ ይነግረኛል ፡ ይሄ ነው የኔ እጣ
  እውነት ትውጣለች ፡ ውሸትን ገልብጣ
  ተከምራ አትቀርም ፡ ተጋግራ እንደ ቂጣ
  እውነት ከውሸት ቤት ፡ አትገባም ተሽጣ
  ተዚህ በላይ እኔ ፡ ምን ላውራ ፡ ምን ላምጣ

  አምሳ ዓመት ስናገር ፡ ሰምተው ጉድ እያሉ
  ሰምተው እንዳልሰሙ ፡ አላየንም አሉ
  ያላወቁ መስለው ፡ ሰው እያጃጃሉ
  እንደ ፍልፈል አፈር ፡ ሰው ሲፈላፈሉ
  ዝም ብለው ተነስተው ፡ የሚቀኑም አሉ
  መደበቅ መታገስ ፡ መያዝ የማይችሉ

  እኛም ሰደድናቸው ፡ አፍረው እንዲተሉ
  ነገሩን ሳያውቁት ፡ እንዲንቀዋለሉ
  ቀሪው እንዲፈራኝ ፡ ውሸት እንዳይሉ
  ኋላ እንዲገባቸው ፡ አድረው እየዋሉ
  ተአላህ እንደሆነ ፡ ስጦታው በሙሉ
  ጥቅም እንደሌለው ፡ ሁሉም በጥቅሉ
  ህዝቡ እየሰማቸው ፡ ሃበሻ በሙሉ
  ልክነው አምነናል ፡ ቶበትን እስተሚሉ
  አርፈው ይቀመጡ ፡ ሰው ተሚያታልሉ
  አላህ አይወደውም ፡ በዚህ ተቀጠሉ
  መታረቅ ይሻላል ፡ መሸመጋገሉ
  ብዙዎች በቅናት ፡ ነደው ተቃጠሉ
  ===============================
  ***    ***    ***    ***    ***
  ===============================
  50 ዓመት ኸደመኝ ፡ ሙሀመድ ኑር ኢሳ
  መድና ወረቀት ፡ ተጁ ሳያነሳ
  ይከትበው ነበረ ፡ ዋሪዳው ሲነሳ
  ተጠንቅቆ ነበር ፡ ቃሌ እንዳይረሳ
  ደከመኝም ሳይል ፡ ለወቅቱም ሳይሳሳ
  እኔ እንደ ሸህ ሁኘ ፡ እሱ እንደ ደረሳ
  የዚህ ሰው ውለታ ፡ መቸም አይረሳ
  ኋላ ታማሚ ሆንኩ ፡ ሰውነቴም ከሳ
  ያዝንልኝ ነበረ ፡ እንዳልሞት ሲሳሳ
  ምግብ አያስበላኝ ፡ ጨጓራው ሲነሳ
  እንገናኝ ነበር ፡ ወይ በራት በምሳ
  አይዞህ ብላበት ፡ ይለኛል ቅመሳ
  ለጀነት ይበለው ፡ ታአላህ ያግኝ ካሳ
  ሁላችን ሟቾች ነን ፡ አጀላችን ደርሳ
  ታሪክ ግን ይቆያል ፡ ተሎም አይረሳ
  ሰው ታላበላሸው ፡ ሃሲድ ታልተነሳ

  ቃልቾቹም ጠሉኝ ፡ ጠጅ ይጠጣል ብለው
  ደብተሮችም ጠሉኝ ፡ ሹም ተጠጋ ብለው
  ባለዛሩም ጠላኝ ፡ ሰው ሄደለት ብለው
  ፉቅራውም ተጠጋኝ ፡ ምን ይፈርዳል ብለው

  ሰምቸ እንዳልሰማሁ ፡ ዝምብዬ መኖር ነው
  ሰውን አውቀዋለሁ ፡ ያበሻ ልምድ ነው
  ቃልቻ ነኝ ብትል ፡ ወየት ተምሮ ነው፧
  ወልይ ነኝ ብትል ፡ ዘሩ ተነማን ነው፧
  ጠንቋይ ነኝ እንዳትል ፡ ሁሉም ሰው ጠንቋይ ነው
  እኔ የምኖረው ፡ እኒህን ችየነው

  ባለዛሩም አያውቅ ፡ ፉቅራውም ፉቅራ ነው
  ባላገሩም አያውቅ ፡ እንደኔ ጃሂል ነው
  እኔን ቅር የሚለኝ ፡ በቃልቾቹ ነው

  አላህ እንደሚሰጥ ፡ ለሚፈልገው ሰው
  አያጠራጥርም ፡ ጥያቄም አይኖረው
  ስጥ አት ስጥ ብሎ ፡ ሰው ለአላህ አያዘው
  ቃልቾች ያውቃሉ ፡ ይሄንን ደህና አርገው
  የሚከራከሩኝ ፡ ታዲያ ለምንድን ነው?
  እኔ ተሰው በላይ ፡ ምንድን አውቄ ነው?
  ወይንስ ተመጽሐፍ ላይ ፡ ገልጨ አንብቤው ነው?
  የሄነን ሁሉ ፍርድ ፡ የምለፈልፈው

  አላህ ላልተማረ ፡ ለእንደኔ አይነቱ ስው
  አላህ ተሙእጅዛው ፡ ጌታችን ቢሰጠው
  አገረ ገዥ ቢሆን ፡ ስልጣን ቢያስጨብጠው
  ሃፍታሙን ደሃ አርጎ ፡ ደሃውን ቢያከብረው
  ታማሚ ስው ቢድን ፡ በሽታው ቢለቀው
  አላህ ይሄን ማድረግ ፡ አይችልም ልንል ነው?

  ይሄን ሁሉ ፍጥረት ፡ አላህ የፈጠረው
  የቱን ሰው ጠይቆ ፡ ማንን አማክሮ ነው?
  እናንተን አማክሮ ፡ ፈቅዳች ሁለት ነው?
  የግሉ የሆነ ፡ አላህ ስልጣን አለው
  ሰው የማይደርስበት ፡ ማነም የማያውቀው
  እኔንም የሰጠኝ ፡ እውቀቱን እሱ ነው
  እናንተ ለፍልፉ ፡ አውነቱ ይሄ ነው

  አንዳንዴስ ይገርማል ፡ እውነታቸውን ነው
  እንደነሱ ሁኘ ፡ እራሴም ባስበው
  በጣም ያስቸግራል ፡ ነገሩ ከባድ ነው
  አሁንም መልሶ ፡ ዙሮዙሮ ያው ነው
  ግን በመጀመሪያ ፡ አላህን ማመን ነው
  ምንም ነገር አይሆን ፡ እሱ ሁን ካላለው
  ቀን ብንደክምበት ፡ ሌት ብንታገለው
  ነገሩም ባይጥመን ፡ ባንወደው ብንጠላው
  ስንዝር አትጨምርም ፡ ያው እጣህ እጣህ ነው
  ተዚህ በተረፈ ፡ ለናንተ ልተወው
===========================
***   ***   ***   ***   ***
===========================
  ዙሪያውን መጡብኝ ፡ በግራም በቀኝ
  እኔ ምን አቅም አለኝ ፡ አላህ ይሁነኝ
  በነ ቄስ ወርቅነህ ፡ በነ መምህር ግርማ
  በአለቃ ውብነህ ፡ ነስር ባላገኝ
  በአለቃ ቀለምወርቅ ፡ በነ ይመር አደም
  ነስር ባላገኝ
  በአለቃ እዮብና ፡ በአውገረድ አለምነሽ
  ነስር ባላገኝ
  እንዴት እሆን ነበር ፡ እስቲ ንገሩኝ?
  እኝህ ተዋርደው ነው ፡ ንጉስ የፈራኝ
  ይሄ ባይሆን ኑሮ ፡ አላህ ባይረዳኝ
  ይኖሩ ነበረ ፡ እንዳዋረዱኝ
  ከክርስቲያኑ እስላም ፡ ነው የጠመመኝ
  ሰው ችላ ስትለው ፡ ያደርግሃል ሞኝ
  ባይኔ እያየኋቸው ፡ የሚያታልሉኝ
  እንዴት ቢንቁኝ ነው ፡ እንዴት ቢደፍሩኝ?
  ስድቡ አልበቃ ብሎ ፡ የሚያዋርዱኝ
  በመውሊድ በለቅሶ ፡ ላይ ስንገናኝ
  ጠጅ ይጠጣል ብለው ፡ ስሜን ሲያጠፉኝ
  እኔም ወድጀ አይደል ፡ አላህ ጥሎብኝ
  እኔም ባልጠጣሁት ፡ እንዴት ደስ ባለኝ
  ሰው ተማወናጅል ፡ ለኔም በረዳኝ
  ግን አላህ ታዘዘ ፡ ተፈረደብኝ
  እኔ ምንድን ላድርግ ፡ ሰዎች ምከሩኝ

  ወይንም እንዳልጠጣው ፡ ዱአ አድርጉልኝ
  እንዳልነካው በጄ ፡ ደግሞ እንዳያምረኝ
  ጠጥቼ አያሰክረኝ ፡ ወይ አያሸናኝ
  የት እንደሚገባ ፡ እኔም አይገባኝ
  ሰውን ቢያስገርመው ፡ ምንም አይገርመኝ
  መጅሊስ ላይ ስቀመጥ ፡ ነው ትዝ የሚለኝ

  ደግሞ ሌላው ነገር ፡ የሚያስገርመኝ
  በሮመዳን ወራት ፡ ትዝም አይለኝ
  ይሄን ስነግራችሁ ፡ መቸም አታምኑኝ
  እንለፍላፊ ሰው ፡ ነው የምታዩኝ

  ያትክልቱን ቦታ ፡ ሚኒሊክ ሰጥቶኝ
  ድህነቴን አውቆ ፡ ሃፍት እንደሌለለኝ
  አቶ ደጃች ሊበን ፡ ወሰደው ቀማኝ
  ፍርድህንም አቁም ፡ ብሎ ላከብኝ
  የምፈራው መስሎት ፡ የምለው ሙጥኝ
  እንዳልናገር ነው ፡ ሰው እንዳይሰማኝ
  ስተቱን ስለሚያውቅ ፡ እንደ በደለኝ
  ሌት ቀን ፡ በዛች መሬት ፡ ሲጨቀጭቀኝ
  ለቅሶዬን ፈጣሪ ፡ ጌታዬ ሰማኝ
  መሬቱን አገኘ ፡ እንደጠየቀኝ
  እሱም ስላረፈ ፡ እኔም አረፍኩኝ

  ነግሬያችሁ ነበር ፡ ፊት ሳልታመም
  ሁሉም እንደሚሆን ፡ ያየሁት በህልም
  ጠጅ እንደምጠጣ ፡ ጫት እንደ ምቅም
  ለፍልፌ ነበረ ፡ ያመነኝ የለም
  በዚህ የሚስማማ ፡ አይኖርም እስላም
  ለቃልቾቹማ ፡ ከባድ ነው ፡ ሸክም
  እንኳን ጠጅ ጠጥቼ ፡ ክልክሉን ሃራም
  ማውራት ይወዳሉ ፡ ወሬ መቀመም
  ጠጅ መጠጣቱ ፡ ክልክል ነው ሃራም
  በቁርዓን በሐዲስ ፡ በዲነል ኢስላም
  አላህ ታዘዘብህ ፡ ሰው መተው አይችልም

  ይችላል ይበለን ፡ ይንገረን አሊም
  ብልሃቱን ይንገረን ፡ መላ ይጠቁም
  ለሱም ሰዋብ አለው ፡ ለኛም አለው ፡ ጥቅም
  እሱ ተሻብህ ግን ፡ አዚዙል ከሪም
  እንደ በሽታ እየው ፡ እንደ መታመም
  ከተለከፈ ሰው ፡ በሽታ ህመም
  ለመዳን ይጥራል ፡ በዶክተር በሃኪም
  መድሃኒት ይወስዳል ፡ በመደጋገም
  ሊድን ይፈልጋል ፡ ተዛ መጥፎ ህመም
  መዳን የማይፈልግ ፡ ንገሩኝ በስም
  እኔ እርግጠኛ ነኝ ፡ አንድ አይገኝም
  እኔም ልዳንና ፡ ልኑር በሰላም

  አላህ በጥበቡ ፡ አላህ በራህመቱ
  ገና ሲወጥነኝ ፡ ሲፈጥረኝ ተጧቱ
  አለኝ ክፉ ዱዓ ፡ የማይበርድ ስለቱ
  ጎራ የማይከልለው ፡ ወንዝና ጅረቱ
  ከፈለኩት ቦታ ፡ ሄደው የሚመቱ
  በሩቅም በቅርብም ፡ የማይሳሳቱ
  ሰዎች ይጠሉኛል ፡ እንዲሁ በከንቱ
  ይከራከሩኛል ፡ እየተሟገቱ
  ቀናተኞች ናቸው ፡ ለወሬ አይታክቱ
  በጣም ይገርመኛል ፡ የአላህ ቸርነቱ
  ይሄን አይነት እጣ ፡ ለኔ መሰጠቱ
  ይቀሙኝ ነበረ ፡ ቢቻል መቀማቱ
  ዝም ብሎ ፡ ያውራ እንጂ ፡ ሁሉም በየቤቱ
  አላህ ስለሰጠኝ ፡ ማን ወንዱ ነክቷቱ
  ትክክለኛው መልስ ፡ ይሄ ነው እውነቱ

  አዱኛ ደህና ሁኝ ፡ እኔ ጋለብኩሽ
  ምስክሬ አንች ነሽ ፡ አዋጅ እንዳትረሽ
  በሃቅ መስክሪ ፡ እንዴኔ እንዳትዋሽ
  የሚያውቀኝ ብዙ ነው ፡ እንዳትወቀሽ
  ብርሃንሽ ሳይጠፋ ፡ ለኛ አጨልመሽ
  እኔን በታች አርገሽ ፡ በላይ ታረገሽ
  ሰው ትመገቢያለሽ ፡ ግን አያጠግብሽ
  በቃኝ የማትይ ፡ የማይጠግብ ሆድሽ
  ማንስ ሃይል ኖሮት ፡ አንችን ሊገፋሽ
  ቢሸሸግ ቢደበቅ ፡ የማያመልጥሽ
  እኛም ልንወድቅ ፡ እሷም ላትሸሽ
  ስሟን ብጠይቃት ፡ አለችኝ ወራሽ
  ስሜን ብትጠይቀኝ ፡ አልኳት ፡ ነኝ ብላሽ
  ኃላ እንዲህ ልትሰድበኝ ፡ ልትለኝ በስባሽ
  ጨካኝ እዝነት የላት ፡ ለትልቅ ትንሽ
  አንች ሰው አትረሽም ፡ ሰውም ቢረሳሽ
  ጊዜሽን ጠብቀሽ ፡ ብቅ ትያለሽ
  በዘጠና ስምንት ፡ ገላችን ፈራሽ
  ውሳኔው ተላይ ነው ፡ ተጌታ ተአርሽ
  አንችም ተልከሽ ነው ፡ አይደለም ወደሽ
  የሁሉም ፈጣሪ ፡ አላህ ነው አዞሽ
  ሂጅና አምጭው ተብለሽ ፡ ሁሴንን ይዘሽ

  ተዘጋጅቻለሁ ፡ እየጠበኩሽ
  እንቺ ተረከቢኝ ፡ ነፍሴን ለሱ አድርሽ
  የሰው ሃብት ፡ የሰው ነው ፡ ይሄን ታውቂያለሽ
  ምን አስለፈለፈኝ ፡ ላንች ምን ጠፍቶሽ
  የመጨረሻ ቃል ፡ ይሄን ልንገርሽ።
  ***    ***    ***    ***    ***
  ***    ***    ***
  ***